Thursday, July 3, 2014

ነገረ ኢትዮጵያ / Negere Ethiopia ዳዊት ሙሉጌታና መሰሎቹ ሰማያዊ ፓርቲን በኢህአዴግ አምባገነናዊ መዳፍ ሥር ለመጣል የተደረገ ሙከራ ኢ/ር ጌታነህ ባልቻ#አብቢን

ዳዊት ሙሉጌታና መሰሎቹ ሰማያዊ ፓርቲን በኢህአዴግ አምባገነናዊ መዳፍ ሥር ለመጣል የተደረገ ሙከራ
ኢ/ር ጌታነህ ባልቻ
(የሰማያዊ ፓርቲ ጥናትና ስትራቴጂ ኃላፊ)
ይህን አጭር ፅሁፍ ለመጻፍ የተገደድኩት በዚሁ ጋዜጣ ሰኔ 18/2006 በቁጥር 459 “በኢ/ር ይልቃል ጌትነት አምባገነናዊ መዳፍ ሥር የወደቀው ሰማያዊ ፓርቲ” በሚል ርዕሰ በወጣት ዳዊት ሙሉጌታ በተሰነዘረው ሀሳብ ዙሪያ የበኩሌን አስተያየት ለመስጠት ነው። ወጣት ዳዊት ሙሉጌታ ሰማያዊ ፓርቲን የተመለከተበትን ዓይን በምንም መልኩ ቢሆን አከብርለታለሁ። ምናልባትም እንድንማርበትና ስህተታችን ምን እንደሆነ ሊያሳየን የፈለገበትን መንገድ እንደዚሁ፤ ነገር ግን በአደባባይ አስተያየቱን ሲያቀርበው ለእኔ ቅንነት ጎድሏቸዋል ብዬ የማስባቸውን እንደሚከተለው አቀርባለሁ። ወጣቱ ምንም እንኳን ከሰማያዊ ፓርቲ እሱ አለኝ የሚለውን ኃላፊነት “በቤተሰብ ምክንያት” ከፓርቲው ለቆ በሩቅ ከሆነ ከአንድ ዓመት በላይ ያለፈው እና ይኼ ጽሁፍ በጋዜጣው ላይ ከመውጣቱም ከአራት ቀናት በፊት ወደ አሜሪካ የተጓዘ ቢሆንም፤ ወደ አደባባይ ላወጣው ጽሁፍ ምላሽ ይሆናል ብዬ የማስበውን ለህዝብ እንዲደርስ ለማድረግ እሞክራለሁ። ዳዊትን የማውቀው አንድነት ፓርቲ አባል በነበርኩበት ወቅት ጓደኛዬ አቶ አርአያ ጌታቸው በሚውዚክ ሜይዴይ ሲያስተምረው ቢሆንም፤ በወቅቱም አርአያ ዳዊት በዛ ለጋ እድሜው የሀገሪቱን የፖለቲካ እንቅስቃሴ ለማወቅ የሚያደርገውን ጥረት ያደንቅለታል፤ ያበረታታውም ነበር። እኔም እንደዚሁ አደርግ ነበር። ያኔም “መርህ ይከበር” ብለን በአንድነት ውስጥ ጥያቄ ስናነሳ ይከታተል እንደነበርም አስታውሳለሁ።
ዳዊት ለጻፈው አስተያየት ምላሽ ለመስጠት ስነሳ ከዳዊት ጋር በየግዜው ያወራናቸውና ያከናወናቸው ተግባራት እያነሳሁ እንደዳዊት ለመዘባረቅ አልፈልግም። የዳዊትን አስተያየት አመክንዮ የለሽነት ፍንትው አድርገው ያሳያሉ ያልኳቸውን ነጥቦች በቅድሚያ ላንሳ። “ኢ/ር ይልቃል ጌትነት አምባገነን መሪ ነው” ሲል የዘረዘራቸው ማጣቀሻ ሀሳቦች ከማንሳቴ በፊት የአምባገነንን ትርጉም ልግለጽ። አምባገነን ማለት ሁሉን ነገር ለማድረግ ኃይል ያለው ወይም በዙሪያው ያሉ ሰዎች እሱ ያለውን ብቻ እንዲፈጽም የሚያስገድድ ማለት ነው። ከዚህ ትርጉም በመነሳትም ኢ/ር ይልቃል አምባገነን ለመሆን፡- 10 የስራ-አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላትና በስራቸው የሚገኙ የቋሚ ኮሚቴ አባላት 37 ቋሚና 13 ተለዋጭ የብሄራዊ ም/ቤት እና 5 የኦዲትና ኤንስፔክሽን አባላትን ያለምንም ተጨማሪ ምክንያት የፈለገውን ነገር በግዳጅ እንዲፈጽሙ ማድረግ ብሎም በነዚህ አካላት ላይ ፈላጭ ቆራጭ መሆን ይችላል የሚል ጭፍን ሀሳብ ይዞ መነሳቱን አንድ በሉልኝ። ይህም ኢ/ር ይልቃል የአምባገነንነት ጉዞ ዳዊት ለማሳየት የፈለገበት መንገድ
1. የፓርቲው አቋም የሚጻረሩ ሀሳቦች በአደባባይ መናገሩ ዋንኛው እንደሆነ የተለያዩ ምሳሌዎችን ጠቅሶ ለመግለጽ ሞክሯል። በመሰረቱ በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 26.1 መሠረት ፓርቲውን በህጋዊ ሰውነት የሚወክለው የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ነው። እሱም ዳዊት የተጠቀሳቸውን ምሳሌዎች የትኛውን የፓርቲውን አቋም እንደተጻረረ አያሳይም። ከዚህ በተጨማሪ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በጠቅላላ ጉባኤ ፓርቲውን በህጋዊ ሰውነት እንዲመራ ለሶስት ዓመት ውክልና ተሰጥቶታል። በዚህ ግዜ ውስጥ ፓርቲውን የሚመጥን ተግባር አላከናወነም ብሎ ብ/ም/ቤቱ ካመነ የትምምን ድምጽ በመንፈግ ጠ/ጉባኤ አስጠርቶ ኢ/ር ይልቃል በሌላ አመራር እንዲተካ አስተያየት ለጠ/ጉባኤው ማቅረብ ይችላል፤ ወይም ኢ/ር ይልቃል በሊቀመንበርነት ሲመርጥ ለፓርቲው የሚመጥን አይደለም ብሎ ሌላ መሪ በማቅረብ ማስመረጥ ይቻላል።
2 “ኢ/ር ይልቃልና ጓደኞቹ የተለየ ሀሳብ ያላቸውንና በአደባባይ ትችት የሚሰነዝሩ አባላት ላይ ጥርሳቸውን ይነክሱባቸዋል፤ ያስፈራራቸዋልም!” የሚል አስተያየት ዳዊት አንስቷል። አስተያየቱ ትንሽ የሚያስገርም፤የሚያስቅም ሆኖ አግኝቼዋለሁ። የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በምንይዘው አመለካከት በፓርቲው አመራሮች በደል ይደርስብናል ካሉ በራሳቸው ላይ ትልቅ ጥያቄ የሚያስነሳ ነው። ኢህአዴግን የሚያህል ‹ሁሉ በጁ ሁሉ በደጁ› የሆነ አምባገነን ስርአት ደፍሮ ለመቃወም ሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ የመጣ ፈርቼ ከመናገር ተቆጠብኩ የሚል ከሆነ በእውነት እጅግ የሚገርምና የሚያሳዝን ነው። ምናልባትም ዳዊት ፅሑፉን ፅፎ ከሀገር ለቆ ለመውጣቱ ምክንያት የሚፈልግ ይመስላል። ከዚህ ይልቅ በዳዊት ጽሑፎች ላይ ጎልተው የሚታዩት ኢ/ር ይልቃልን አምባገነን መሪ የሚያስብል አስተያየት ሳይሆን በተለያየ ወቅት ለሰማያዊ ፓርቲ ድጋፍ የሰጡ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ለማለያየት የተሰነዘረ መርዘኛ ሀሳብ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። ይኸውም የሙስሊሞች ጥያቄ ፖለቲካዊ እንጂ ሀይማኖታዊ አይደለም፤ ኦሮምኛ በላቲን ፊደል ሳይሆን በግእዝ ነው መጻፍ ያለበት፤ አማራ የሚባል ብሄር የለም፤ እና ሌሎች መሰል ሀሳቦች ኢ/ር አንስቷል ብሎ በአስተያየቱ ላይ አካቷል።
ዳዊትን ሳውቀው በዕድሜው ልጅ ቢሆንም እንደዚህ አይነት ሁለት ስለት ያላቸው መርዛማ ቃላቶች ከብእሩ ይተፋል ለማለት ግን ህሊናዬን ይከብደዋል። ሆኖም ግን ኢ/ር ይልቃል የሙስሊሞች ጥያቄ ፖለቲካዊ ነው ሲል በሀገሪቱ ውስጥ የእስላም መንግስት ይቋቋም ለማለት ፈልጎ እንዳልሆነ ግልጽ ነው። የሙስሊም ኢትዮጵያውያን ጥያቄ የመብት ጥያቄ ነው። መብት የማክበርን የማስከበር ጥያቄ ደግሞ የዜጎች ፖለቲካዊ ጥያቄ ነው። የኦሮምኛ መጻፊያ ፊደላት በግእዝ ይሁን ማለት ከላቲን ፊደል ይልቅ ሀገር በቀል የሆነውን የግእዝ ፊደል ብንጠቀም ይሻላል ማለቱ እንደሆነ ሳትረዳው እንዳልቀረህ ይሰማኛል። ዳዊት ከላይ ባነሳቸው አስተያየቶች የኢ/ር ይልቃልን አምባገነንነት ወይም አላዋቂነት ምኑ ላይ እንደሆነ ባለማየቴ ግን አዝኛለሁ። በሁለተኛ ደረጃ በዳዊት በተደጋጋሚ ግዜ የተነሳውን ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ያለውን ግንኙነት በተመለከተ የሰነዘረው ሀሳብ ነው። ዳዊት ሰማያዊን ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር በግድ የማዋሀድ ቅዠቱን ሌሎች አባላት ላይ ወስዶ የብዙሀኑ ፍላጎት እንደሆነ ይገልጻል። ቅዠቱም እውን ያልሆነው በኢ/ር ይልቃል ሴራ ነው ብሎ ይደመድማል። ለዚህ መደምደሚያው እንዲረዳው አንቶ ፈንቶ ወሬዎችን ካነሳው ሀሳብ ጋር በማይዛመድ መልኩ ይዘባርቃል። (ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር በማዋቀር የሚደረጉ ግንኙነቶችን በተመለከተ ፓርቲው በመርህ ደረጃ የሚያምንበት፤ ከዚያም አልፎ ከሌሎች ጋር የመስራት ጥያቄ ምንም እንኳን ስልጣን ባይኖረውም ለጠቅላላ ጉባኤው ውሳኔ የሚረዳ ግብአት ለማምጣት ሲባል በፓርቲያችን ውስጥ በተለያየ ግዜ ሰፊ ውይይቶችንና ክርክሮች ተደርገዋል። ከነዚህ ውስጥ እኔ ከአቶ የሺዋስ አሰፋ ጋር አባላት በተገኙበት ያደረግነው ክርክር 38 ለ 12 በሆነ አብላጫ ድምጽ ሰማያዊ አሁን ባለበት ሁኔታ ራሱን ችሎ እንዲንቀሳቀስ የሚያሳስበው ሀሳብ ገዢ ሆኗል። ከስድስት ግዜ በላይ በፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ አባላት በኩል ለውይይት በአጀንዳነት ቀርቦ ከተከራከርን በኋላ ከአጠቃለይ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት መካከል ከሁለት ሰው በላይ ድጋፍ ሊያገኝ አልቻለም። እንዲሁም ለብሄራዊ ም/ቤቱ ከሶስት ግዜ በላይ ይኼው አጀንዳ የቀረበ ሲሆን በሁሉም ስብሰባዎች ላይ አሁን ሰማያዊ ባለበት ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ብቻውን እራሱን ያጠናክር የሚለው ሀሳብ በሰፊ የድምጽ ድጋፍ ገዢ ሀሳብ ሆኖ እየተሰራበት ይገኛል። ይኼንንም ከቃለ ጉባኤዎቹ ማረጋጋጥ ይቻላል።)
ዳዊት ይህን አስተያየት ሲሰነዝር ግንዛቤ መውሰድ የነበረበት ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር መዋቅራዊ ግንኙነት የሚፈልጉ ሰዎች እንዳሉና ሀሳቡ ጤናማ እንደሆነ እንደሚያምነው ሁሉ በተቃራኒው ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር መዋቅራዊ ግንኙነት ለማድረግ አሁን ሰማያዊ ፓርቲ ግዜው አይደለም የሚሉ ሰዎች ሀሳብ ለማክበር መዘጋጀት ነበረበት። አለመፈለግም አሉባልታና ውሸት የሚያስነዛ ሳይሆን በዴሞክራስያዊ መርሆች መሰረት የማይፈልገውንም ሀሳብ በአብላጫ ድምጽ ለመርህ ሲባል የሚያከብረው መሆኑን የሚዘነጋው አይመስለኝም። በሶስተኛ ደረጃ የዳዊት ጽሑፍ የምመለከተው በተለየ መልኩ ነው። ጽሁፉን በተደጋጋሚ ሳነበው ልረዳው የቻልኩት ዋንኛ ነጥብ ዳዊት በርዕሱ ላይ “በኢንጅነር ይልቃል አምባገነናዊ መዳፍ ሥር የወደቀውን ሰማያዊ ፓርቲ” በሰፊው ለማስረዳትና ለመዳሰስ የፈለገ አስተያየት ሳይሆን “በኢህአዴግ አምባገነናዊ መዳፍ ስር ሰማያዊ ፓርቲን ለመጣል የተደረገ ሙከራ” ሆኖ አግኝቼዋለሁ።
ዳዊት አስተያየቱን ሲሰጥ ለሰማያዊ ፓርቲ ተቆርቁሮ ፓርቲውን “ከቁልቁለት ጎዳና” ለማዳን የሚሰማውን አስተያየት ጽፎታል ብዬ ለመረዳት ብችል ዛሬ ብእሬን ለማንሳት አልሞክርም ነበር። ይልቁንም ብዙ የምንማርበትን ነጥብ ነቅሼ ለማውጣት በቻልኩ ነበር። ነገር ግን በዳዊት ጽሁፍ ውስጥ ሰማያዊ ፓርቲ በሀገሪቱ ዋንኛ ተፎካካሪ ፓርቲ እንዳይሆን ኢህአዴግ የጀመረው ማደናቀፍ ተግባር ፍንትው አድርጎ አሳይቶኛል። ከዚህ የኢህአዴግ የማደናቀፍ ስራ በመነሳት የዳዊትን ጽሑፍ ለመዳሰስ የፈለኩበትን የተለያዩ ነጥቦች በማንሳት በሰፊው ለመዳሰስ እሞክራለሁ። ኢህአዴግ የሰማያዊ ፓርቲ ጉዞን ማደናቀፍ የጀመረው ገና ከጨቅላነቱ አንስቶ ነው። ይኸውም ፓርቲው የመሥራች ጉባኤውን ለማካሄድ ያደረገውን ጥረት መሰብሰቢያ አዳራሾችን ማግኘት እንዳይችል በማድረግ አስተጓጉሏል፤ በተከራየነው የጽህፈት ቤት ግቢ ውስጥ ድንኳን ጥሎ ለማከናወን የተደረገውን ጥረት የቤቱ አከራይ እንዲከለክል እንዲሁም ቤቱን እንዲያስለቅቅ ብሎም ስብሰባው እንዳይካሄድ የተሞከረ ቢሆንም በአደራጆቹ ብርቱ ጥረት ጉባኤው ተካሂዷል። ቀጣይ ችግር የተፈጠረው ከብሄራዊ ምርጫ ቦርድ የህጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ ሰርተፍኬት ለመስጠት የተፈጠረው ጋሬጣ ነበር። ይኼኛውም ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ በወር ውስጥ የሚያልቅ ጉዳይ ስምንት ወር አቆይተው የእውቅና ሰርተፍኬት ተሰጥቷል። ሆኖም የኢህአዴግ ዋንኛ ፍላጎት ማዳከምና ማሰላቸት ሲሆን በነገሩ ተሰላችተው በአቅም ማጣት ይበተናሉ፤ በተለይ የገንዘብ ድጋፍ ሊያደርጉ ይችላሉ የሚሏቸውን ደጋፊዎችና አባላት በማስፈራራት ሥራውን ማስተጓጎልም ሞክረዋል። በአይበገሬዎቹ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች የፓርቲው ችግር ችግራቸው ሆኖ የኢህአዴግን ህልም ቅዠት ሆኖ እንዲቀር አድርገዋል። ምንም እንኳን ኢህአዴግ ግን ይኼ ሁሉ ጥረት እንዳልተሳካለት ቢያውቅም እኩይ ድርጊቱን ከማከናወን ራሱን ሊገታ አልቻለም። ከመጀመሪያው ሰማያዊን የማደናቀፍ የእጅ አዙር ሙከራ በኋላ በቀጥታ የገባው የፓርቲው አባላትና አመራር የደህንነት መዋቅሩን በመጠቀም ለእሱ እንዲሰሩ በጥቅም ለመደለል ከፍ ሲልም ማስፈራራት የሞከረ ሲሆን (አሁን ሳስበው አንዳንዶች ለዚህ ሰለባ ሆነው ይሆናል፤) ሆኖም የፈለገውን ፓርቲውን የማዳከም ጥረት ማሳካት ግን አልተቻለውም። ከዚህ ሲያልፍ የጀመረው ሰማያዊን የማዳከም ጥረት በፓርቲው አመራር ቦታ ላይ የራሳቸውን ሰው የማስረግ ሥራ ሲሆን ይኼኛውም በሚፈልጉት መልኩ የሚሳካላቸው አልመሰላቸውም።
ስለዚህ የመጨረሻው ወደሆነው ሰማያዊን የማክሰም ሂደት ራሳቸውን ከተዋል። ሰማያዊን የማክሰም ዋንኛ ተግባር ጅማሬ የሚነሳው በስም ማጥፋት በአሉባልታ ሲሆን ለዚህ ማሳያውም ዳዊትን የቀድሞ የሰማያዊ ፓርቲ የወጣቶች ጉዳይ ም/ኃላፊ እንዲሁም ከኢ/ር ይልቃል ጌትነት ጋር በተደጋጋሚ ሚስጥር ሳይቀር የሚያወሩ ጓደኛሞች አድርጎ ራሱን ማቅረብ ነው። ይህ ሁኔታ ደግሞ ይበልጥ የፓርቲው ቅርብ ሰው መሆኑን ለመግለጽ የረዳው አስመስሏል። በዚህም የሰማያዊ ጠንካራ የድጋፍ መሠረቶች ለሆኑት
1 የእስልምና እምነት ተከታዮች
2 አማርኛ ተናጋሪ ዜጎች
3 ኦሮምኛ ተናጋሪ ዜጎች (ከመሬት መስፋፋት ጋር በተያያዘ ሰማያዊ በያዘው አቋም )
4 ከ70 በመቶ በላይ ለሚገምተው የኢትዮጵያ ወጣት
5 በሴቶች
6 ከከተማ አካባቢ የሚኖሩ ዜጎች
7 በቅንነት ዜጎች ፓርቲዎች ተባብረው እንዲታገሉ የሚፈልጉ ደጋፊዎች በጥርጣሬ አይን እንዲታይ ግጭት የሚያስነሱ ሀሳቦች እንደ አቋም ፓርቲው እንደያዘ አድርጎ ለማሳየት ሞክሯል።
የገንዘብ አጠቃቀሙ ግልጽ የሆነ በኦዲተር የሚመረመር፤ በፓርቲው ኦዲትና ኢንስፔክሽን የተረጋገጠ የሂሳብ አሰራር ያለው፤ በተፈለገ ግዜ ሊጣራ የሚችል ጉዳይን በግድ እመኑኝ ለማሰኘት ሲባል በረቂቅ ዘዴ ገንዘብ ተሰርቋል ለማለት ዳዊት መድፈሩ አሉባልታ ለመንዛት የሄደበትን ርቀት ያሳያል። በሌላ በኩል ኢህአዴግ በተለያየ ግዜ ሰማያዊ ፓርቲ ሊያከናውን የሞከረውን የተቃውሞ ሰልፍ በተደጋጋሚ በተለያየ ምክንያት ሲያደናቅፍ፤ በተጨማሪም በቅርቡ ዳዊት እንደ ምሳሌ ያቀረበውን “400” ሰዎች ብቻ የተገኙበት የተቃውሞ ሰልፍ እንዴት እንደተከናወነ በወቅቱ እኔ የኢህአዴግ አፈና ሰለባ ስለነበርኩ እኔ ከምናገረው ሌሎች ድርጊቱን የተከታተሉ ሁሉ የሚፈርዱት ሁኔታ ቢሆን ይሻላል። ነገርግን ይህንን ነገር የሰማያዊ ፓርቲ ውድቀት አድርጎ ማሳየት የተፈለገበት መንገድ ነገሩን ከኢህአዴግ ጫንቃ ላይ ለማውረድ የሞከረና ብሎም የስም ማጥፋት ዘመቻው ከማን ጋር የተሳሰረ እንደሆነ የሚያሳይ ነው። ይኼው የዳዊት የሰማያዊ ፓርቲ ውድቀት የመሻት አባዜ ሌላ ቅጥፈት እንዲመዝ አስችሎታል። ይህም የፓርቲውን የአባላት ብዛት ሊያውቅ የሚችልበት ምንም መንገድ ሳይኖረው በድፍረት በአሁኑ ሰአት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ብዛት አራት ሺህ ነው ብሎ ይናገራል። ከላይ በዘረዘርኳቸው አመክንዮዎች መሰረት ዳዊት በሰማያዊ ፓርቲ ላይ ህዝብ ጥሎት የነበረውን እምነትና ድጋፍ እንዲሸረሽርና በጥርጣሬ እንዲያየው፤ ግፋ ሲልም በተቃዋሚ ፓርቲዎች ላይ የትላንት መጥፎ ትዝታው እንዲቀሰቀስ ለማድረግ የነዛው አሉባልታና የስም ማጥፋት ተግባር ኢህአዴግ የጀመረው ሰማያዊን የማክሰም ክፍል ሁለተኛ ምእራፍ የሚያንደረድር የድብቅ ሴራ አካል ነው። የኢሀአዴግ ሁለተኛ ምእራፍ የመጨረሻ ክፍል የሚሆነው ከሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ ፓርቲያችን በኢ/ር ይልቃል ጌትነትና በጥቂት ግለሰቦች ቁጥጥር ስር ውሏል፤ እናድነው! የሚል ሌላ ሀይል ከፓርቲው ውስጥ እንዲነሳ ማድረግ ሲሆን፤ ተከትሎም እንደፈለገ በሚዘውረው ምርጫ ቦርድ በኩል ቀድሞ ቅንጅትና ኦብኮ ፓርቲዎች ላይ እንዳደረገው የሰማያዊን ሰርተፍኬት ለነዚህ ሀይሎች መስጠት መፈለጉን ያመላክታል።
በዚህ ሂደት እንቅፋት ሊሆኑ የሚችሉትን ኢ/ር ይልቃል ጌትነትና ሌሎች የፓርቲው አባላትን ከማዋከብ እስከ ማሰር የሚደርስ እርምጃ በመውሰድ፤ በዚህም መጪውን ምርጫ ኢህአዴግ በ2007 ምርጫ ሥጋት የሚሆንበትን ሰማያዊ ፓርቲ ከምርጫ ለማስወገድ የሚያደርገው ጥረት መጀመሩን ከአጠቃላይ የዳዊት ጽሁፍ መገንዘብ ችያለሁ። መቼስ ‹ቀን እባብ ያየ ማታ በልጥ በረየ› ቢሆንም ዳዊት እኔ በፍጹም በዚህ መልኩ አስቤ አስተያየት አልሰጠሁም ቢለኝ በፓርቲው ውስጥ የሚነሱ ምንም አይነት ቅሬታ ማስተናገድ የሚችል መዋቅርና መድረክ ያለው ድርጅት ውስጥ ጥያቄዎችን ወይም ቅሬታዎችን አምጥተህ እንዲታዩና እንድንወያይበት ቢያደርግ ኖሮ ምናልባት አስተያየቱን ከቅን መንፈስ ለመመልከት በቻልኩ ነበር።
ነገር ግን ዳዊት አሁን የፈጸመው ተግባር ማንን ለመጥቀም እንደሆነ በተረዳሁት መጠን ገልጫለሁ።ይህ ባይሆንማ ኖሮ ከአንድ ዓመት ከሦስት ወር በፊት ፓርቲውን በቤተሰብ ምክንያት ለቅቄያለሁ ብሎ ደብዳቤ ፅፎ የለቀቀ አባል እስከ አሁን ፓርቲው እያከናወናቸው ያሉትን ተግባራትና የቅርብ ጊዜ ስብሰባዎች ጭምር በማንሳት ፓርቲውንና ሊቀመንበሩን ለማሳጣት ሙከራ ባላደረገ ነበር። በመጨረሻም ዳዊት ያቀረበው አስተያየት ባያስደንቀኝም ለሀገራችን የዴሞክራሲ ሥርአት ግንባታ በምናደርገው ጥረት ከውስጥም ከውጭም ከፍተኛ ተግዳሮቶች እንደሚገጥሙን የምናውቅና የምንጠብቀው ጭምር በመሆኑ ዳዊትንም ሆነ ከዳዊት ጀርባ የሚገኙ ግለሰቦችንና ተቋማትን አይሳካላችሁምና አትልፉ ልላቸው እወዳለሁ።
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

No comments:

Post a Comment