Friday, June 20, 2014

የታሪካችን ክፋይና የዚህ ትውልድ አንድ ገጽታ የሆነን ጉዳይ በማዳፈንና የባህር በር ጥያቄ ማንሳትን በትምክህት አስተሳሰብና በተቃዋሚ ጎራ የሚያስፈርጅ በማስመሰል የሚገነባ አገርም መኖር የለበትም፡፡ አገር የሚገነባው በትውልድ ቅብብሎሽ ነው እስከተባለ ድረስ እያለፈ ያለው ትውልድ ‹‹አሰብ የሚባል የባህር በር ነበረህ›› እያለ ልጁንና ወንድሙን ማስተማሩ አይቀሬ ነው፡፡ ስለሆነም በአሰብ የባህር በር ጥያቄና በጋራ ተጠቃሚነት ጉዳይ ላይ በናይል ቤዝን ኢኒሼቲቭ እንደተደረገው ያለ ምክክር፣ ውይይትና ድርድር ብቻ ሳይሆን ትኩረት መስጠት ያሻል፡፡ ይኼ ደግሞ የኢሕአዴግ ብቻ ሳይሆን የዚህ ትውልድ አደራ ነው፡፡

አዎ እኔም የእብድ የቃውስ የሸርሙጣ ትርጉም ለነፃነት የሚታገሉ ኢትዮጵያዊነትን የሚሰብክ ግፈኞችን የሚታገል…ለኢትዮጵያዊነት የሚኖር ከሆነ አዎ እብድ ነኝ አዎ ቀውስ ነኝ አዎ ሸርሙጣ ነኝ እላቸዋለው፡፡
በባህር በር ጉዳይ ላይ የሚያተኩር ውይይትና ድርድር ያስፈልጋል
በጉተማ ዘለዓለም
በቅርቡ የባህር በር ጉዳይና የኢትዮጵያ ዕጣ ፈንታን አስመልክቶ በአንድ ፀሐፊ የቀረበ ሐሳብ ተስተናግዶ አንብቤያለሁ፡፡
በእውነቱ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ኃላፊነት እንወስዳለን የሚሉ ወገኖችም ሆኑ ‹‹በቀጣዮቹ ሦስትና አራት አሥርት ዓመታት አገሪቷ ከድህነት አወጣለሁ!›› ብሎ የተነሳው መንግሥት ይህን ጉዳይ ወደ ጠረጴዛ በማምጣት መፈተሽ ያለበት ጊዜ ይመስለኛል፡፡ የባህር በር ባለቤትነት ጉዳይ የታሪክ፣ የሕግና የጂኦግራፊ ብቻ አይደለም፡፡ ለመሆኑ ከአገሪቱ አጠቃላይ ምርት (GDP) ሲሶ ያህሉን ለወደብ ኪራይ እይገበሩና በሌሎች አገሮች በጎ ፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ የወደብ አጠቃቀም ላይ ተጣብቆ እንደምን ይኖራል? የአገሪቱን ዕድገት እንዴት በተከታታይ ለማረጋገጥ ይቻላል? የሚል ጥያቄ ማስቀደም እሻለሁ፡፡
በአንዲት የአሳ አጥማጅ መንደር በአፋር ቀይ ባህር ጠረፍ አካባቢ የተወለዱትና በተማሪዎች እንቅስቃሴም ሆነ በአገሪቷ ጉዳይ የነቃ ተሳትፎ የነበራቸው አምባሳደር የሱፍ ያሲን ከጥቂት ዓመታት በፊት በካናዳ ሐዋርያ ከሚባል ጋዜጣ ጋር በዚህ ጉዳይ ላይ ቃለ ምልልስ አድርገው ነበር፡፡ ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች አንዱ ታዲያ ‹‹አሰብ የኢትዮጵያ የባህር በር ነች›› ብሎ የሚያምን ትውልድ ይመጣ ይሆን የሚል ነበር፡፡
ጥያቄውን ሲመልሱም፣ ‹‹ለእኔ እስከሚገባኝ ድረስ አሰብን ማስመለስ ማለት ወያኔ የኤርትራን ነፃነት ተቀበልኩና ሪፈረንደም አካሄድኩ የሚለው ሐሳብ ትቶ በታሪክ፣ በሕግና በጂኦግራፊ አከራካሪ ያልሆነውን የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የመቀበል ጉዳይ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ሲቀጥሉም በፊት በፊት ይኼ የነፍጠኞችና የአፋሮች ጥያቄ ነበር፡፡ የአሰብ ጉዳይ ዛሬ በአብዛኛዎቹ የትግራይ ተወላጆች ብቻ ሳይሆን፣ ከሕወሓት የተገነጠለው ቡድን መሪዎች ጥያቄ እየሆነ መጥቷል፡፡ ‹‹ከድንበር›› ጦርነት በኋላ መለስ ዜናዊ እንኳ ኤርትራን ነፃ የማውጣት ተጋድሏቸውን እንደ ታላቅ ጀብዱ እየተኩራሩ መናገር አቁመዋል ብለው ነበር፡፡
‹‹በአገሪቱም ዛሬም ድረስ በተቆርቋሪነት አሰብ አሰብ የሚሉ ወገኖች እየበዙና ደጋፊ እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ እነዚህ ወገኖች አሁን አገሪቷን እየመራ ያለው ኃይል ምን አቋም እንዳለው ሳይገነዘቡ ቀርተው ሳይሆን፣ ለአገሪቱ ዕድገትና ለጂኦስትራቴጂ ጠቀሜታ ወሳኝ የሆነውን የባህር በር ጥያቄ በኢትዮጵያ ሕዝብ ልብ ውስጥ እንዲሰርፅ ለማድረግ ይመስለኛል፡፡ በነገራችን ላይ ኤርትራ ለ62 ዓመታት በጣሊያን ቅኝ ግዛትነት ከቆየች በኋላ እንደገና ከእናት አገሯ ጋር የተቀላቀለችው በኤርትራ ሕዝብ ተጋድሎ፣ በነበረው መንግሥት ዲፕሎማሲያዊ ርብርቦሽና በነበረው ዓለም አቀፋዊ ሁኔታ አመቺነት ነው፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች እስካሉ ድረስ ነገም ቢሆን ጉዳዩ የተዘጋ አይደለም፡፡ ስለዚህ እውነታው አይታሰቤና አይሞከሬ የሆነ የህልመኞች መፈክር አይደለም፡፡ በዚህ ሒደት ግን ለአንድነቱ የሚታገለው የአፋር ሕዝብ በዚህ ትግል ውስጥ የሚኖረው ወሳኝ ሚና በቀላሉ የሚታይ አይደለም፤›› ነው ያሉት አምባሳደር የሱፍ፡፡
ዛሬም ድረስ ያለው አገራዊ ሁኔታ የባህር በር እጦት ቁጭትና በተለይም አሰብ የኢትዮጵያ ሕጋዊ ይዞታ ነው የሚል ስሜት የተላበሰ መሆኑን ስንገነዘብ በእርግጥም የአምባሳደሩን አባባል ትክክለኛነት እንረዳለን፡፡ በአሁኗ ኢትዮጵያ ከነጉድለታቸው የተቃውሞ ጎራውን የተቀላቀሉ ሁሉም ኃይሎች አንድ የሚያደርጋቸው ጥያቄ የአሰብ ጉዳይ ነው፡፡ ከሞላ ጐደል አብዛኞቹ የግል ጋዜጣ ኤዲቶሪያሎች ይኼንን ሐሳብ ያስተጋባሉ፡፡ በጉዳዩ ላይ ሰፊ የውይይት መድረክ ለመፍጠር ፍርኃት የቀፈደዳቸው የትምህርትና ሥልጠና ተቋማት ስለበዙ እንጂ ምሁራን በሹክሹክታ ከሚናገሯቸው ሚስጥሮች አንዱ ይኼው ነው፡፡
በኤርትራ የነፃነት ጥያቄ ላይ በቀዳሚነት በ1954 ዓ.ም. ነፍጥ ያነሳው ጀበሃን ጨምሮ ሻዕቢያና ሌሎች የፖለቲካ ኃይሎች ከኢትዮጵያ ለመገንጠል ረጅም ጦርነት አካሂደዋል፡፡ ይህ ክስተት ሙሉ በሙሉ የኤርትራን ሕዝብ ድጋፍ ያገኘ ነበር (በተለይ ዛሬ ላይ) ባይባልም፣ የንፁኃንን ሕይወት ያረገፈና የአገርን ኢኮኖሚ ያደቀቀ ሆኖ አልፏል፡፡
አንዳንዶች ያን የጦርነት ምዕራፍ እንደ ሶሪያ ባዝ ፓርቲና የናስሯ ግብፅ ያሉት ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች በሙሉ ኃይል እንደደገፉት ይገልጻሉ፡፡ በእርግጥ ሊቢያ፣ ሱዳንና ኢራን የመሳሰሉ ኃይሎችም ድጋፍ ቀላል አልነበረም፡፡ መረጃዎች እንደሚያስረዱት እነዚህ ኃይሎች በኤርትራ ውስጥ እጃቸውን ያስገቡት ኤርትራ ውስጥ ሙስሊሞች ስለሚኖሩ ሳይሆን፣ ሁለተኛውን የዓለም ጦርነት ተከትሎ በመጣው የቀዝቃዛው ጦርነት የመጀመርያ ፍጡራን ካደረጋቸው መካከል ‹‹ነፃ›› መንፈስ የተላበሰች ኤርትራ እንድትካተት በመፈለጉ ነው፡፡ ይህንን ቀዳዳ በቀላሉ በመጠቀም የዓረብና የሙስሊም ጎረቤቶች እጃቸውን አስገብተዋል፡፡
አሁን ከ23 ዓመታት በኋላም ቢሆን የኤርትራ መገንጠል ቅቡልነት ያገኘ ያልመሰለበት አንዱ ምክንያት በውጭ ኃይሎች ተፅዕኖና በኤርትራና በኢትዮጵያ መንግሥታት ተቀባይነት እንጂ በሕዝብ ለሕዝብ ትክክለኛ ውሳኔ የተፈጸመ ባለመሆኑ ነው፡፡ ኤርትራ የኢትዮጵያ አካል ነች የሚለው አወዛጋቢ ጉዳይ ለጊዜው ይቅርና ‹‹የአሰብ የባህር በር ተጠቃሚነት ሙሉ መብት የኢትዮጵያ ነው›› የሚለውን ሀቅ ራሳቸው የሻዕቢያ አምባገነን መሪዎች ልባቸው የሚነግራቸው ይመስላል፡፡ ለአባባሉ ጥሩ ማሳያ ሊሆን የሚችለው ዛሬም ድረስ የአሰብን ወደብ ለኢራን (አክራሪ ዓረብ አብዮተኛ አገር) በኪራይ ስም ሙሉ መብት በመስጠት ሌላ ጠላት ፈጥራ ፍጥጫ ውስጥ የከተተችን በመሆኗ ነው፡፡
ኤርትራ ውስጥ ያለው በሐማሴን፣ በአካለ ጉዛይና በሠራኤ ያሉትን ጨምሮ ‹‹የብሔረሰብ ለውጥ›› የተደረገባቸው ቢመስሉም፣ የአገሪቱ ሕዝብ የኢትዮጵያ አካል ሆኖ የኖረ በተለይም የትግራይ ማኅበረሰብ አካል ነው፡፡ ዶ/ር ሀብተ ማርያም አሰፋ የተባሉ የሕግ ምሁርና የዚሁ ማኅበረሰብ አባል፣ ‹‹የኢትዮጵያ ታሪክ ጥያቄዎችና ባህሎች›› በተሰኘው የምርምር ሥራ የጠቀሱትን ማየት ይቻላል፡፡
‹‹በ19ኛው ምዕተ ዓመት መገባደጃ ላይ በበርኑ የአፍሪካ ቅርምት ጉባዔ ላይ የአውሮፓ ተቀራማች ቅኝ ገዥዎች በነሲብ በካርታው ላይ ባሰመሩት መስመር በሁለትና በሦስት መንግሥታት መካከል ካቆራረጧቸው አንጡራ አፍሪካዊያን ብሔረሰቦች አንዱ ትግሬዎች ወይም ትግራዊ ብሔረሰብ ነው፡፡ በተለምዶ በመሀል አገር ትግሬ ተብሎ የታወቀው ብሔረሰብ በ1890 ላይ ጣሊያኖች ኤርትራ የተባለችውን ኮሎኒ በመሠረቱበት ወቅት ከመረብ ወዲያ ባህረ ነጋሽ፣ ከመረብ ወዲህ በትግራይ የነበረውን አንድ ሕዝብ ነው ለሁለት የከፈሉት፡፡ ከ50 ዓመታት በኋላ የጣሊያን ቅኝ ገዥዎች ኤርትራን ለቀው በሚወጡበት ጊዜ ይህ ሕዝብ አንድ የነበረውን የቀድሞ የጋራ መጠሪያ ብቻ ሳይሆን ባህሉን፣ ሥነ ልቦናውንና ትስስሩን አልመለሰም፤›› ነበር ያሉት፡፡
ነገሩ አወዛጋቢ ቢመስልም የአሰብ የባህር በር ብቻ ሳይሆን የኤርትራ ሕዝብ የኢትዮጵያ አካል ነው ብሎ መናገር የሚያስደፍረውም ይኼ ሀቅ ነው፡፡ በእርግጥ ከአፄ ምንሊክ አገዛዝ አንስቶ እስከ ደርግ ሥርዓት መውደቅ ድረስ እንደ ሌሎች ብሔሮች ሁሉ የትግራይ ማኅበረሰብ ከአገራዊ ተሳትፎና ጥቅሙ የተገፋበት ሁኔታ እንደነበር መካድ አይቻልም፡፡ ሻዕቢያም ሆነ ሕወሓት/ኢሕአዴግ ነፍጥ አንሰተው ሥርዓት ለመቀየር የሞት ሽረት ትግል ያደረጉበት ዋነኛው ምክንያትም ይኼው ወደ ዳር የመገፋትና መገለል ክስተት በመንሰራፋቱ ነበር፡፡
ኢሕአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግሥት የኤርትራ ነፃነት ጥያቄን ደግፎ የአሰብ ይገባኛል ጥያቄን በመግፋት ለኤርትራ ጥቅም አንድ ዕርምጃ ሄዶ ተባብሯል የሚሉ ተቺዎች ብዙዎች ናቸው፡፡ በእርግጥም በተለይ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ይኼንኑ ሐሳብ በሚስማማ አኳኋን ‹‹ሌላ ግማሽ ክፍለ ዘመን ደም ለመፋሰስና ለመዋጋት የሕዝቦችን ፍላጎት በግድ አንገፋም፡፡ የኤርትራ የነፃነት ጥያቄ ተቀብሎ ከማስተናገድና ፊታችንን ወደ ውስጥ ጉዳዮቻችን ከማዞር ውጪ አማራጭ የለንም፤›› ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ እስካሁን እስካለው የኢሕአዴግ ኃይል ድረስ የተያዘው አቋም ይኼው መሆኑ ይታወቃል፡፡
እንደ ብዙዎቹ የአገራችን አንጋፋ ፖለቲከኞችና ምሁራን በአሰብ ጉዳይ ላይ ቁጭታቸውን የገለጹት ኢንጅነር ኃይሉ ሻውል በ‹‹ሕይወቴና የፖለቲካ ዕርምጃዬ›› መጽሐፍ ገጽ 80 እንዲህ ብለዋል፡፡
‹‹የአሰብን ወደብ ማጣትና የአፋር ሕዝብ የመከፋፈሉ ጉዳይ ሁልጊዜ የሚያሳዝነኝና የሚከነክነኝ ነው፡፡ በእኔ ግምት አሰብን ማጣት የኢትዮጵያ ህልውና ዋጋ እንደማጣት ነው፡፡ ዘግተንም ያየነው ይህንን ነው፡፡ በ1997 ዓ.ም. ሆነ ከዚያም በፊት ከሕዝቡ ጋር ባደረግነው ውይይት ይኼ ቁጭት በብዙኃኑ ውስጥ ያለ ነው፡፡ ለኤርትራ መገንጠል አገላጋይ ነው ከሚባለው አሜሪካዊ ከኸርማን ኮኸን ጋር በዚሁ ጉዳይ ላይ ለመወያየትም ሞክሬ ነበር፡፡ በ1982 ዓ.ም. ድርድር ወቅት የአሰብ ወደብ ጉዳይ እንዴት እንደተወሰነ ስጠይቀውም ‹በአሰብ ወደብ ጉዳይ የኢትዮጵያ ሕዝብ የአሜሪካን መንግሥት በኃላፊነት እየወቀሰ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ቀስ በቀስ አሜሪካ በኢትዮጵያውያን የተጠላች አገር እንዳያደርጋት ሥጋት አለኝ› በማለት ገለጸልኝ፡፡
በአሰብ የባህር በር መብታችን ጉዳይ ያሉ ሰነዶችንና የምሁራንን አስተያየት መመርመር፣ በጉዳዩ ላይ ውይይትና ድርድር ለመጀመር መነሳሳት የሚያስፈልግበት ጊዜ ላይ የምንገኝ ሆነናል፡፡ በመሠረቱ ኢሕአዴግም ቢሆን በኢትዮጵያ አዲስ ታሪክ ውስጥ ከተጫወተው ሚና አንፃር እውነታውን ወደ ጎን ሊገፋው አይችልም፣ አይገባምም፡፡ የአሰብን ጉዳይ እንዳላለቀለት የታሪክ ምዕራፍ በመቁጠር ‹‹ውሾን ያነሳ…›› ማለቱም መቆም አለበት፡፡
በመሠረቱ በራሱ ኢሕአዴግ መሪዎቹና አባሎቼ በሚላቸው ዜጎች ውስጥ ስንቶቹ የአሰብ ወደብ የባለቤትነት መብታችንን እንደሚቀበሉ ያውቃሉ? በግልና በቡድን ከሚካሄዱ የተናጠል ውይይቶች ባሻገር በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ያሉ ‹‹የኢሕአዴግ አባላት›› ሳይቀሩ ሲወያዩ የባህር በር ጥያቄና የአሰብ ጉዳይን ደጋግመው ማንሳታቸው (በቅርቡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መነሳቱን ልብ ይሏል) ለምን ችላ ይባላል?
የታሪካችን ክፋይና የዚህ ትውልድ አንድ ገጽታ የሆነን ጉዳይ በማዳፈንና የባህር በር ጥያቄ ማንሳትን በትምክህት አስተሳሰብና በተቃዋሚ ጎራ የሚያስፈርጅ በማስመሰል የሚገነባ አገርም መኖር የለበትም፡፡ አገር የሚገነባው በትውልድ ቅብብሎሽ ነው እስከተባለ ድረስ እያለፈ ያለው ትውልድ ‹‹አሰብ የሚባል የባህር በር ነበረህ›› እያለ ልጁንና ወንድሙን ማስተማሩ አይቀሬ ነው፡፡ ስለሆነም በአሰብ የባህር በር ጥያቄና በጋራ ተጠቃሚነት ጉዳይ ላይ በናይል ቤዝን ኢኒሼቲቭ እንደተደረገው ያለ ምክክር፣ ውይይትና ድርድር ብቻ ሳይሆን ትኩረት መስጠት ያሻል፡፡ ይኼ ደግሞ የኢሕአዴግ ብቻ ሳይሆን የዚህ ትውልድ አደራ ነው፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጹሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

No comments:

Post a Comment