Monday, June 30, 2014

ከምእራብ እና ምስራቅ ወለጋ የተፈናቀሉ የአማራ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ፍትህ አሁንም ድረስ አለማግኘታቸውን ገለጹ፤

ከምእራብ እና ምስራቅ ወለጋ የተፈናቀሉ የአማራ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ፍትህ አሁንም ድረስ አለማግኘታቸውን ገለጹ፤
ከምእራብ ወለጋ ዞን ከጊምቢ ወረዳ እንዲሁም ከቀሌም ወለጋ ዞን የተፈናቀሉ የአማራ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ንብረታቸው ተዘርፎ ከአካባቢው እንዲወጡ ከተደረገ በኋላ፣ ችግራቸውን ለአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዲሁም ለፌደራሉ መንግስት ቢያመለክቱም የሚሰማቸው ማጣታቸውን ገልጸዋል።
ኢሳት ካነጋገራቸው የተፈናቃዮች ተወካዮች መካከል አንዳንዶች እንደገለጹት «የአማራ ክልልም ሆነ የፌደራሉ መንግስት በክልሎች ጉዳይ ጣልቃ አንገባም» በሚል ምክንያት ለጥያቄያቸው መልስ ለመስጠት ፈቃደኞች አልሆኑም። ከመንግስት የሚሰጠው መልስ ተስፋ እንዳስቆረጣቸውም ተፈናቃዮች ገልጸዋል።
የተፈናቃይ ተወካዮች እንደሚሉት ከፍተኛ ችግር ከነበረበት ከሚያዚያ 22 እስከ ግንቦት2 በነበረው ጊዜ ለደረሰው የሰው ህይወት እንዲሁም ለጠፋው ከፍተኛ ንብረት የአካባቢው ባለስልጣናት እና በክልሉ ተሰማርቶ የሚገኘው ልዩ ሃይል እጅ አለበት። ባለስልጣናቱ የችግሩ አሳሳቢነት ሲነገራቸው መልስ ለመስጠት ፈቃደኞች ባለመሆናቸው ከፍተኛ ውድመት እንዲደርስ ምክንያት መሆኑን የተፈናቃዮች ተወካዮች ተናግረዋል።
በተለይም ጉዳዩን እንዲያጣራ በቅርቡ የተቋቋመው አጣሪ ኮሚቴ ማስረጃዎችን አስቀድሞ ይፋ እያደረገና የምስክሮችንና የጠቋሚዎችን ስሞች አስቀድሞ ይፋ እያደረገ ህዝቡ በድጋሚ እንዲጋጭ ጥረት እያደረገ ነው በማለት ተወካዮች ገልጸዋል። በጊምቢና በቄለም ያሉ ዘመዶቻቸውን በስልክ ለማግኘት መቻላቸውን የሚናገሩት ተፈናቃዮች፣ አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ ዛቻና ማስፈራራቱ እንደቀጠለ መሆኑን እንደነገሩዋቸው አስረድተዋል።
ከኦሮምያና ከፌደራል የተውጣጡ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ማክሰኞ ወደ ጊምቢ በማቅናት ነዋሪውን እያነጋገሩ ነው። እስካሁን ድረስ በመንግስት በኩል ተፈናቃዮችን በተመለከተ የተሰጠ ይፋዊ መግለጫ የለም። በጊምቢ ተነስቶ በነበረው ግጭት የአንድ ሰው ህይወት ሲወድም፣ አንድ ፎቅና ሁለት መኖሪያ ቤቶች ተቃጥለዋል፤ በርካታ ቤቶችም ተዘርፈዋል።
~~ምንጭ zehabesha.com~~

No comments:

Post a Comment